May 13, 2013 02:25 am By Leave a Comment
በቀረጥ፣ በሙስናና ባለስልጣናትን የንግድ ሸሪክ በማድረግ ኢትዮጵያን እየጋለቡዋት ያሉ “ባለሃብቶችና አሽከሮቻቸው” እስካልተነኩ ድረስ ኢህአዴግ በሙስና ላይ የጀመረውን ትግል ሙሉ ሊያደርገው እንደማይችል ተገለጸ። ጅማሮው የችግሩ ቁልፍና እምብርት በሆነው ተቋም ላይ መሆኑ የሚደነቅ እንደሆነ የሚገልጹ ክፍሎች ደግሞ ድሩ ያልተበተበው የለምና የመጨረሻው አካሄድ ወዴት እንደሚያመራ ለመገመት ቢቻልም ጅምሩ ይገፋል የሚል ጥርጣሬ እንዳላቸው አስታውቀዋል።
የባለስልጣናት ሚስቶችን፣ ዘመዶችና ወዳጆችን በተቋሞቻቸው ውስጥ በማይመጥኑት ሃላፊነት በመመደብ፣ ከተለያዩ የማማለያ ሽልማቶች ጋር ከፍተኛ ደሞዝ በመክፈል፣ አንዳንዴም ውጪ አገር ድረስ የህክምና ወጪ በመሸፈን ሰበብ የአገሪቱን የአመራር በትር ጨብጠው አገሪቱን እያለቡ ያሉት ወገኖች በይፋ እንደሚታወቁ የሚገልጹ ክፍሎች “አሁን ተጀመረ የተባለውና ይፋ የተደረገው የሙስና ትግል እነዚህን ክፍሎች ብብቱ ስር ይዞ የሚቀጥል ከሆነ ከቀልድ አይዘልም” ሲሉ ጥርጣሬያቸውን ያስቀምጣሉ።
አትራፊ የሆኑ የህዝብና የአገር ተቋማትን ወደ ግላቸው ያለ ክፍያ፣ ያለ ተመጣጣኝ ዋጋ፣ በተጭበረበረ ጨረታና አሰራር ወደ ግላቸው በማዞር አቶ መለስ “ተራው ህዝብ” በማለት በሚጠሩት ህዝብ ትከሻ ላይ እንዳሻቸው የሚዘሉትን “የሙስና አባቶችን” መታገል የማይችል የጸረ ሙስና ቀረርቶ ከተራ የፖለቲካ ልዩነት የዘለለ መነሻና መድረሻ ሊኖረው እንደማይችል እነዚሁ ወገኖች ይናገራሉ።