Wednesday, May 15, 2013

ግንቦት 7 - ታሪካዊ ቀን




በግንቦት 7/1997 ምርጫ 524 የምክርቤት ወንበሮች ለምክር ቤት ቀረቡ፡፡ 23 የሚሆኑት በነሐሴ ወር በሱማሌ ክልል ለሚደረገው ምርጫ ወደጎን ተተዉ፡፡

ግንቦት 7 በተካሄደው ምርጫ ተሳትፌያለሁ፡፡ ማን ይናገር የነበረ፤ ማን ያርዳ የቀበረ እንደሚባለው ያየሁትን፣ የሰማሁትን፣ የተሳተፍኩበትን ነው የማቀርበው፡፡ እኔ የዚህ መጽሐፍ ደራሲ በሦስተኛ ሰው አድርጌ ታሪኩን ላቀርበው ሞክሬ፤ ራቀብኝ፣ ባዕድ ሆነብኝ፣ የኔ መስሎ አልሰማህ አለኝ፡፡ እናም ታሪኩን በቀጥታ ለመተረክ ወሰንኩ፡፡

ግንቦት 7/1997 ከጠዋቱ 12 ሰዓት ከቤቴ ወጥቼ ወደምርጫጣቢያ አመራሁ፡፡ ከምኖርበት ሰፈር ወደምመርጥበት ጣቢያ ለመሄድ ከ15 እስከ 20 ኪ.ሜ. መንዳት ነበረብኝ፡፡ በጠዋት የተነሳሁትም አንድም ቀደም ብዬ ከመረጥኩ በኋላ ከተማውን ተዘዋውሬ ለማየት እንዲረዳኝ በማሰብ ነበር፡፡ ዘጠኝ ኪሜ ያህል ተጉዤ መገናኛ አካባቢ ስደርስ ከአንድ የምርጫ ጣቢያ ፊትለፊት ረዥም ሰልፍ አየሁ፡፡ መኪናዬን ትንሽ ቆም አድርጌ ሰልፉ ምን ያህል ረዥም እደሆነ ለመቃኘት ሞከርኩ፡፡ ሰልፉ እየተጠማዘዘ ቢያንስ 300 ሜትር የሚያክል ቦታ ይዟል፡፡ የተሰለፈውን የሰው ዓይነት ለማየትም ሞከርኩ ዝንቅ ነበር፡፡ ወንድ/ሴት፣ ትልቅ/ትንሽ፣ ወጣት/አዛውንት ሁሉም በትዕግስት ተሰልፈው ይጠብቃሉ፡፡ እንዴት በጥዋት ሊነሱ ቻሉ ብዬ እያሰብኩ መንገዴን ቀጠልኩ፡፡ መገናኛ አደባባዩጋ ስደርስ ወደሰሜን አቅጣጫ ወደሚወስደው መንገድ ወደቀኝ ታጠፍኩ፡፡ ወደ እንግሊዝ ኤምባሲ ወደሚወስደው መንገድ፣ በድሮው አጠራር ወይዝሮል ወደሚባለው መንገድ ወደሚያስገባው አደባባይ ደርሼ ወደግራ ታጠፍኩ፡፡ ከዚህ ቦታ ጀምሮ ምርጫ የማደርግበት ሰፈር እስከምደርስ ድረስ ስድስት ወይም ሰባት የምርጫ ጣቢያዎች አየሁ፡፡ ሁሉም ቦታዎች እጅግ በጣም በርካታ ሰዎች ተሰልፈው በትዕግስት ይጠባበቃሉ፡፡ እንደዕንቁ ጠብቀው ያቆዩት የምርጫ ካርዳቸውን ከሳጥናቸው ለመጨመር በጉጉት ይጠብቃሉ፡፡

መጀመሪያ እንዳየሁት የምርጫ ጣቢያው ሁሉ ሌሎች ቦታዎችም የተሰለፉት ዓይነት ተመሳሳ ነበር፡፡